የኢትዮጽያ ሳይንስ አካዳሚ የኢትየጵያ 6ኛው ሀገራዊ ምርጫ ቅድመ-ምርጫ ህዝባዊ ውይይት አካሄደ::

ግንቦት 18 ቀን 2013 (ኢሳአ)፡ 6ኛው ሀገራዊ ምርጫን በማስመልከት ከታሪክ፣ ከሰላምና መረጋጋት እንዲሁም ከህግ አንጻር ለመዳሰስ የኢትዮጽያ ሳይንስ አካዳሚ የኢትየጵያ 6ኛው ሀገራዊ ምርጫ ቅድመ-ምርጫ ህዝባዊ ውይይት በኢንተር ኮንቲኔንታል ሆቴል አዲስ አበባ በስብሰባ አዳራሽ እና በኦንላይን አካሂዷል፡፡

በውይይቱ ላይ ሶስት አንጋፋ ሙሁራን ከታሪክ፣ ከሰላምና መረጋጋት እንዲሁም ከህግ አንጻር ምርጫን በማስመልከት የመነሻ ጽሁፍ አቅርበዋል፡፡ ፕሮፌሰር ባህሩ ዘውዴ ‹ምርጫ በኢትዮጵያ ታሪካዊ ዳሰሳ›፣ ፕሮፌሰር ካሳሁን ብርሃኑ ‹መጪው ምርጫ ለሰላምና መረጋጋት ያለው እንድምታ› እንዲሁም ዶ/ር ጌታቸው አሰፋ ‹ምርጫና ሰላም፤ የተቋማትና የህግ ሚና› በሚል ርዕሰ-ጉዳዮች ዙሪያ ጥናታዊ ትንታኔ አቅርበዋል፡፡

ፕ/ር ባህሩ ዘውዴ የምርጫን ታሪክ በዳሰሱበት ጽሁፋቸው ከአጼ ኃይለስላሴ ጊዜ ጀምሮ እስካአሁን ድረስ ኢትዮጵያውያን ሀቀኛ፣ ነጻ፣ ፍትሃዊና ሰላማዊ ምርጫ ለማድረግ ያደረጉት ጥረት አልተሳካም ብለዋል፡፡ ፕ/ር ባህሩ በዚህም ምክንያት መጪው 6ኛው ሀገራዊ ምርጫ ብዙ ተስፋ የተጣለበት ሊሆን ችሏል ብለዋል፡፡   ‹ያም ቢሆን ታዲያ አሁንም ምርጫው በብዙ ተግዳሮቶች የተከበበ በመሆኑ ጥያቄው ይህ ምርጫ የአዲስ ምዕራፍ መጀመሪያ ወይስ ተጨማሪ ችግሮችን የሚያመጣ ነው?› ብለዋል፡፡

ፕ/ር ባህሩ አበክረው እንደገለጹት ምርጫውን ማካሄድ አማራጭ የሌለውና ከምርጫው የሚገኘው ዋነው ፍሬ ነገር ውጤቱ ሳይሆን ሂደቱ ነው ብለዋል፡፡ ምርጫው የዴሞክራሲያዊ ሂደት በኢትዮጵያ እንዲጀመር ማድረጉ ነው ቁምነገሩ ብለዋል የታሪክ ተመራማሪው፡፡

ምርጫን ከሰላምና መረጋጋት ጋር ጥናታዊ ጽሁፍ ያቀረቡት ፕ/ር ካሳሁን ብርሃኑ በበኩላቸው በኢትዮጵያ እስካሁን ድረስ የምርጫ ግርግር እንጂ ትክክለኛ ምርጫ ተካሂዶ አያውቅም ብለዋል፡፡ 6ኛው ሀገራዊ ምርጫ ምንም እንኳን የተለያዩ ጉድለቶች ቢኖሩበትም ነጻ፣ ፍትሃዊና አሳታፊ እንዲሆን በብርቱ መጠንቀቅና መስራት እንሚገባ አስገንዝበዋል፡፡ ፕ/ር ካሳሁን ‹ይህ ካልሆነ ግን መዘዙ የከፋነው፤› ሲሉ አሳስበዋል፡፡ 

በፕ/ር ካሳሁን ብርሃኑ እምነት የ6ኛው ሀገራዊ ምርጫ ውጤትን ተከትሎ ህጋዊነትና ተቀባይነት ያለው መንግስት ይመሰረታል፡፡ በዚህም ምርጫው የመንግስትና የመስተዳድርን ህጋዊነት ጥያቄን በተመለከተ በየቦታው የሚንጸባረቀውን ውዝግብን ይቀርፋል፡፡ ይህ ደግሞ ሰላምና መረጋጋትን በአገሪቱ ሊያሰፍን እንደሚችል እምነታቸው መሆኑን የአለምአቀፍ ግንኙነትና የፖለቲካ ተመራማሪው ፕ/ር ካሳሁን ብርሃኑ ተናግረዋል፡፡

ምርጫና ሰላም፤ የተቋማትና የሕግ ሚና በሚል ርዕስ መነሻ ጽሁፍ ያቀረቡት ዶ/ር ጌታቸው አሰፋ አለመታደል ሆኖ ነው እንጂ ምርጫ የስጋት ምንጭ ሳይሆን የችግሮች መፍቻ መሳሪያ መሆን ነበረበት በማለት በቅድመ-ምርጫ፣ በምርጫ ቀንና ከምርጫ ቦኃላ የምርጫ ሂደትን የሚያደናቅፉ በርካታ ሁኔታዎችን ዘርዝረዋል፡፡

ዶ/ር ጌታቸው አሰፋ  ቅድመ-ምርጫ፣ የምርጫ ቀንና ከምርጫ ቦኃላ ያሉ ሁኔታዎችን ያገናዘበ የሰላምና የደህንነት አሰራሮች በሚመለከታቸው አካላት በተቃናጀና በተናበበ መልኩ ሊዘረጉ እንደሚገባ አስገንዝበዋል፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የፍርድ ቤቶች አሰራርና ውሳኔ ገለልተኛ እየሆነ መምጣቱን የሚያሳዩ ምልክቶች መታየታቸው አበረታች የህግ አሰራር እየተዘረገ መሆኑን ያመላክታል ሲሉ የህግ ባለሞያው ዶ/ር ጌታቸው አሰፋ ተናግረዋል፡፡

የመነሻ ጽሁፍ አቅራቢዎቹን ትንታኔ ተከትሎ በስብሰባ አዳራሹና በበይነ-መረብ በርካታ አሰተያየቶችና ጥያቄዎች ቀርበው ውይይቱን አዳብረዋል፡፡ የኢትዮጵያ ሳይንስ አካዳሚ በምርጫው ዙሪያ ቀጣይ ህዝባዊ ውይይቶችን እንደሚካሂድ የኢሳአ ስራአስፈጻሚ ዳይሬክተር ፕ/ር ተከተል ዮሀንስ ተናግረዋል፡፡

የቅድመ-ምርጫ ህዝባዊ ውይይቱን  ቪዲዮ ለመመልከት ከስር ያሉትን ማስፈንጠሪያዎች ይጫኑ